Friday 16 May 2014

ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተ ክርስቲያን

መጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ

ብዙዎች ኢየሱስ ክርስቶስን ቤተ ክርስቲያን እንደማትሰብክ አድርገው ለማቅረብ ይሞክራሉ፤ ነገር ግን ሐዋርያዊት የኾነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ስለክርስቶስ ያላስተማረችበት ጊዜ የለምም አይኖርም፤ ደግሞም እናት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በጊዜያችን አንዳንዶች መናፍቃን የኢየሱስን ክብር አሳንሰው ከአብ በታች አድርገው እንደሚያስተምሩት ሳይኾን በእውነት ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ክብሩ የተካከለ፣ ቅድመ ዓለም የነበረ አኹንም ያለና ዓለምን አሳልፎ የሚኖር፤ ለፍርድ ዳግመኛ የሚመጣ፤ እውነተኛ ፈራጅ የአማልክት አምላክ የነገሥታት ንጉሥ ነው ብላ የምታስተምረው፡፡ ይኽ ብቻ ሳይኾን ሥጋውን ደሙን በምትሠዋበት በቃል ኪዳን ታቦቱም ላይ “ኢየሱስ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር ሕያው” (የሕያው የአብ የባሕርይ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ) ብላ አክብራ ስሙን ትጽፋለች እንጂ በድፍረት ሆና ስሙን መቀለጃ አታደርግም፡፡