Saturday 4 January 2014

ሰበር ዜና ነገ እሑድ በሺዎች የሚቆጠሩ ምእመናን የሀ/ስብከቱን የተቋማዊ ለውጥ ጥናት በመደገፍ በ8፡00 ወደ መንበረ ፓትርያርኩ ሊተሙ ነው

የአ/አ ገዳማትና አድባራት ሰበካ ጉባኤያት ሊቃነ መናብርት፣ ካህናት፣ ሰንበት ት/ቤቶችና ምእመናን የሀ/ስብከቱን የተቋማዊ ለውጥ ጥናት በመደገፍ ነገ እሑድ በ8፡00 ወደ መንበረ ፓትርያርኩ በሺዎች ሊተሙ ነው፤ የአደረጃጀትና አሠራር ጥናቱ ጸድቆ እንዲተገበርና የሙሰኛ አስተዳዳሪዎችና ተቃዋሚ ነን ባዮች የሀብት ምንጭ እንዲመረመር ይጠይቃሉ

‹‹ምእመናን የቤተ ክርስቲያን አባላት እንጂ አካላት አይደሉም›› ባዮቹና በተቃውሟቸው ‹‹መንግሥት እየደገፈን ነው›› ያሉት እነኃይሌ ኣብርሃ÷ ፓትርያርኩ ረዳታቸውን ‹‹እስከ ገና ድረስ ዘወር የማያደርጉ›› ከኾነ እንቅስቃሴያቸው ትጥቃዊ መልክ እንደሚኖረው በማስጠንቀቅ ዝተዋል። በተጨማሪም የሚከተለውን የማስፈራሪያ ዛቻ መሳይ መልእክት ለማስተላለፍ ሞክረዋል – ‹‹ያኹኑ ሊቀ ጳጳስ የማን ረዳት ናቸው፤ የማኅበረ ቅዱሳን ናቸው ወይስ የቅዱስነትዎ? በሊቀ ጳጳሱ ፈረጅያ ሥር ተከተው ጀግና ሊቀ ጳጳስ በሠራው ሀ/ስብከት ቢሮ ተሰጥቷቸው እያረቀቁበት ስለኾነ እንዲወጡ ይደረግልን! ከአቅማችኹ በላይ ከኾነ አሳልፋችኹ ለመንግሥት ስጡ፤ ሄደን እኛ እናስለቅቀዋለን፤ ውጊያ ከመገባቱ በፊት ወረቀቱ ተቀዶ መመለስ አለበት፤ እነንቡረ እድ ኤልያስ እነአባ ሰረቀ ያርቅቁ፡፡ ታኅሣሥ ገና ላይ ረዳት ሊቀ ጳጳሱ ወደ ጅማቸው ብቻ ቢሄዱ፤ ይህን ከተማ አበጣብጠውታል፤ መንግሥትም ስለማይናገር ነው እንጂ እያዘነ ነው፤ ረዳትዎን ዘወር ያድርጉልን!››

በተጨማሪም በግፍና ነውር በተሞላው አስተዳደራቸው የተነሣ የወሊሶ ካህናትና ምእመናን ያባረሯቸው አቡነ ሳዊሮስ የቅ/ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤን ውሳኔ በመጋፋት ከተቋማዊ ለውጥ ተቃዋሚዎች ጋራ መቆማቸውን በይፋ አረጋግጠዋል – ‹‹በጣም ደስታ ተሰምቶኛል፤ እኔ በፊት ብቻዬን የኾንኩ ይመስለኝ ነበር፤ ግን ወደ ኋላ ከተመለሳችኁ እናንተ ናችኹ የምትመቱት፤ ቀደም ሲል ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን በነበሩ ሰዓት መልካም አባት ነበሩና ሲዋጉ ሲያደባድቡ የነበሩ ሰዎች እነርሱ ናቸው፤ ቅዱስ አባታችን በነርሱ ነው ተቃጥለው የሞቱት፤ እናንተ ያልተናገራችኹት ነገር የለም፤ ሙሉ ቀን ብትናገሩ ደስ ይላል፤ ንግግራችኹ ሁሉ ጥሩ ነው፤ ግን ሰዎቹ ምንድን ነው በአቋራጭ ቤተ ክርስቲያኒቱን ተረክበው እንደፈለገ ሊያደርጉ ነበር፤ እናንተ ባትነቁ ኖሮ ባቋራጭ ሊረከቧት ነበር፤ ቤተ መንግሥቱንም ቤተ ክህነቱንም ተረክበው እኛን እንደ ውሻ እንጀራ ሊጥሉልን ነው፤ እንደዚህ ነው ዓላማቸው ብዙዎቻችን አልገባንም እንጂ፤ ስለዚህ ቅዱስ አባታችን መልስ ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ይህ ካልኾነ ወደ ሌላ አቅጣጫ እንደሚሄድ ነው እያሳዩ ያሉት፤ ቅዱስ አባታችን፡፡ እና እንዳትመለሱ ነው አደራ የምላችኹ፡፡›› /አቡነ ሳዊሮስ የእነኃይሌን እብሪት በማሞጎስ በፓትርያርኩና በስምንት ሊቃነ ጳጳሳት ፊት ከተናገሩት/ 

ፓትርያርኩ ለአደረጃጀትና አሠራር ጥናቱ ክንውን ከሰጡት አባታዊ መመሪያ በተፃራሪ በእነ ኃይሌ ኣብርሃ ለሚመራው የተቃዋሚ ነኝ ባይ ወሮበላ ስብስብ ፊት በመስጠት የሚያሳዩት የመደራደር ዝንባሌ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱና በተቋማዊ ለውጥ ኃይሎች ትዝብት ውስጥ ጥሏቸዋል፤ ‹‹ተጠርቼ መጥቼ የእርስዎ ረዳት የኾንኩትና ደፋ ቀና የምለው የቅ/ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤን ውሳኔና የቅዱስነትዎን መመሪያ ለማስከበር ነው፤ አቋምዎን በግልጽ ያሳውቁኝ!›› /ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ/