Saturday 12 April 2014

አዎ ማኅበረ ቅዱሳንን ተጠንቀቁ! ትልቁ ስጋት እሱ ነውና


በአዲሱ ተስፋዬ

መነሻ

ይህንን ጽሁፍ ለመጻፍ ያነሳሳኝ ሰንደቅ ጋዜጣ በሚያዝያ 1/2006 ዓ.ም እትሙ ማኅበረ ቅዱሳንን በተመለከተ ያወጣው ቃለ መጠይቅና ሀተታ ነው [i] :: ሶስቱም አስተያየት ሰጭዎች “ማኅበረ ቅዱሳን አክራሪ ነው:: ስለዚህም መንግስት ሊያፈርሰው ነው ” የሚለው ወቅታዊ ዜና ምንጩ ከየት እንደሆነ ግልጽ እንዳልሆነ ጠቅሰዋል :: በፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ አቶ አበበ ወርቁ ጉዳዩን “በሬ ወለደ ነው” ብለው ሲያጣጥሉት ፣ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ ደግሞ ” የዚህ ወሬ ምንጩ ከየት እንደሆነ አናውቅም” ሲሉ ተመሳሳይ ነገር ተናግረዋል።