Monday 18 February 2013

አባ ፓምቦ

ቅድስት ሜላኒያ ስለ አባ ፓምቦ እንዲህ አለችው "ገና መጀመሪያ ጌዜ ከሮም ወደ እስክንድርያ ስመጣ የእርሱን ቅድስና ሰምቼ እንዲሁም አባ ኤስድሮስ ስለ እርሱ ነገረኝና ከዚያም እርሱ ወዳለበት ወደ በረሃው ወሰደኝ። እኔም በሳጥን ውስጥ የታሸገ ሦስት መቶ (300) ወቄት ወርቅ ወሰድኩና የሚፈልገውን ያክል እንዲወስድ ለመንኩት። እርሱ ግን ከተቀመጠበት ሳይንቀሳቀስ ሰሌን እየታታ ባረከኝና "እግዚአብሄር ዋጋሽን ይሰጥሽ ዘንድ ፈቃዱ ይሁን" አለኝ። ከዚያም ረድኡን "ይህን ውሰደውና በሊቢያና በደሴቶች ለሚኖሩት ወንድሞች ለሁሉም አከፋፍላቸው፣ እነዚህ ገዳማት ከሌሎቹ ይልቅ ድሃዎች ናቸውና" አለው። በግብጽ ላሉት ግን  የእነርሱ መሬት የተሻለ ለምነት ስላለው ምንም እንዳይሰጥ አዘዘው።

እኔ ግን ስለ ስጦታዬ የበለጠ እንዲያከብረኝና እንዲያመሰግነኝ ተስፋ በማድረግ እዚያው ቆምኩ። ሆኖም ምንም ሲለኝ ስላልሰማው፣ አባ ውስጡ ምን ያህል እንዳለ ታውቅ ዘንድ 300 ወቄት ነው አልኩት። እርሱ ግን እራሱን እንኳ ቀና ሳያደርግ "ያመጣሽለት እርሱ፣ ልጄ ሆይ፣ መጠኑን የሚነግረው አያስፈልገውም። ተራሮችን የሚመዝን እርሱ የዚህን ወርቅ ክብደት የበለጠ ያውቀዋል። የሰጠሺው ለእኔ ቢሆን ኖሮ በእርግጥ መንገርሽ አግባብ ነበረ። የሰጠሽው ለእግዚአብሄር ከሆነ ግን የመበለቲቷን ሁለቱን ሳንቲሞች ያልናቀ እርሱ ያውቀዋልና መንገር አያስፈልግሽም" አለኝ። ከጥቂት ጊዜ በኋላ ምንም ሳይታመም ቅርጫት እየሰራ እያለ በሰባ ዓመቱ ዐረፈ። ሊያርፍ ሲል እየሰራ የነበረውንና ሊያልቅ ትንሽ የቀረውን ቅርጫት ላከልኝ፣ እንዲህ በማለት፣ "ታስቢኝ ዘንድ በእጆቼ የተሰራውን ቅርጫት ተቀበዪ፣ ታስቢኝ ዘንድ የምተውልሽ ሌላ ምንም ነገር የለኝምና።" ስጋውን ለመቃብር ካዘጋጀው በኋላ ቀበርኩትና ከበረሃው ተመለስኩ። ያቺን ቅርጫትም እስከ ህይወቴ ፍጻሜ ድረስ በክብር አኖርኋት።

ይህ አባ ፓምቦ ሊሞት ሲል እንዲህ አለ ፦ "ወደዚህ በረሃ ከመጣሁበትና በአቴን ሠርቼ በዚህ መኖር ከጀመርኩበት ጊዜ አንስቶ በእጄ ያልሰራሁትንና ያልደከምኩበትን ነገር አልተመገብኩም፣ የምጸጸትበት ቃል አልተናገርኩም። ሆኖም ሃይማኖተኛ መሆን ገና ምንም እንዳልጀመረ ሰው ሆኜ ነው ወደ እግዚአብሄር የምሄደው።"

የአባታችን የአባ ፓምቦ ምልጃውና በረከቱ አይለየን። አሜን።

(ከበረሓውያን ሕይወትና አንደበት በዲ/ን ያረጋል አበጋዝ)
ጥር 2003 ዓ.ም

ክርስቲያኑ ኢትዮጵያዊ መብቱን ለማስከበር ያልቻለባቸውና የማይችልባቸው ምክንያቶች


ይህ ጽሑፍ የአቅማቸውን ጥቂት ነገር ለማድረግ የሚተጉትን ላይመለከት ይችላል።

(ደጀ ሰላም የካቲት 8/2005፤ ፌብሩዋሪ 15/2012/ PDF)፦ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአገራችን በኢትዮጵያ እየተስፋፋ በመጣው እምነትን በነጻ የማራመድ መብት ገፈፋ ዋነኛ ተጠቂ ከሆኑት ኢትዮጵያውያን መካከል ኦርቶዶክሱ ክፍል ዋነኛ ተጠቃሽ ነው። በወታደራዊው የደርግ ዘመን የነበረውን ግፍና መከራ እንኳን ለጊዜው ብናቆየው “የሕዝብ ብሶት ወለደኝ” ያለው የኢሕአዴግ መንግሥት ከተመሠረተ ወዲህ ቤተ ክርስቲያናችን በዓይነ ቁራኛ ከመታየት እስከ የ“ነፍጠኛ ጎሬ” እስከመባል ድረስ ብዙ ዘለፋ አስተናግዳለች። ከዚያም ገፋ ሲል በአንዳንድ አክራሪዎች ምእመናኗ ታርደዋል፣ አብያተ ክርስቲያናት ተቃጥለዋል፣ ከየአካባቢው እንዲፈናቀሉ ተደርገዋል። ለዚህም በስልጣን ላይ ያለው ፓርቲ የሚያራምደው ፖሊሲ ሁነኛ ምክንያት ነው።