Thursday 31 October 2013

ተሀድሶያውያን ‹‹ ቅዱስ አትናቴዎስ የወንጌል አገልግሎት›› የሚል የእምነት ተቋም ሊያቋቁሙ ነው

(አንድ አድርገን ጥቅምት 21 2006 ዓ.ም)፡- THE ETHIOPIAN HERALD TUESDAY 29 OCTOBER 2013 ዕትም ገጽ 7 ላይ ይህን ነገር ይዞ ወጥቷል ፡፡

Notice 

“KIDUS ATNATEWOS YEWENGEL AGELEGELOT” has applied use this name as a religious institution. Any individual or organization opposing the name is here by requested to report to the Ministry of Federal Affairs and Religious Organization and Association Registration directorate, Office on November 11/2013 at 9:00 AM

Ministry of Federal Affairs
Notice
“KIDUS ATNATEWOS YEWENGEL AGELEGELOT” has applied use the under indicated symbol.


(ቅዱስ አትናቴዎስ የወንጌል አገልግሎትየሚል መስቀል ያለው ክብ ምልክት)Any individual or organization opposing the symbol is here by requested to report to the Ministry of Federal Affairs and Religious Organization and Association Registration directorate, Office on November 11/2013 at 9:00 AM
Ministry of Federal Affairs

ይህን ለመታሰቢያዬ አድርጉት በዲ/ን ህብረት የሺጥላ Yihen Lemetasebiaye Aderegut by D/n Hibret Yeshitela



Wednesday 30 October 2013

የሌለውን ፍለጋ -ክፍል አንድ

በዳንኤል ክብረት


አቡነ ተክለ ሃይማኖትና አቡነ ኤዎስጣቴዎስ( ጎርጎራ፣ ደብረ ሲና ማርያም)

ተስፋየ ገብረ አብ ‹የስደተኛው ማስተዋሻ› የተሰኘ መጽሐፍ ማውጣቱንና ባነበው መልካም እንደሆነ ገልጦ አንድ ወዳጄ ‹ስስ ቅጅውን› ከሀገረ አሜሪካ ላከልኝ፡፡ ከዚህ በፊት ሌሎች መጻሕፍቱን አንብቤያቸዋለሁ፤ በአጻጻፍ ችሎታው የምደሰተውን ያህል እንደ አበሻ መድኃኒት ነገሩን ሁሉ እርሱ ብቻ የሚያውቀው ምስጢር ስለሚያደርገው፤ በአንዳንድ ጉዳዮችም ሆን ብሎም ሊያናጋቸው የሚፈልግ ኢትዮጵያዊ እሴቶች ያሉ ስለሚመስለኝ፤ ተስፋዬ ለምን እንደዚህ ይጽፋል? እያልኩ የምጠይቃቸው ነገሮች ነበሩ፡፡

በዚህ መጽሐፉ ውስጥም ያንን ጥርጣሬየን አጉልቶ ሥጋ ነሥቶ እንዳየው የሚያደርገኝ ነገር ገጠመኝ፡፡ ተስፋየ በገጽ 306 ላይ ‹‹የፍስሐ ጽዮን ፖለቲካ› በሚል ርእስ ስለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የማያውቀውን ነገር ጽፏል፡፡ ስለማያውቀው ነገር የጻፈው ባለማወቁ ብቻ አይመስለኝም፡፡ አንድም ለማወቅ ባለመፈለጉ፣ አለያም ሆን ብሎ የማፍረስ ዓላማ ይዞ ይመስለኛል፡፡
ይህን የምለው በሁለት ምክንያት ነው፡፡ ተስፋዬ ስለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ለመጻፍ ሲፈልግ ሊያነባቸው የሚችላቸው መጻሕፍት በምድረ አውሮፓ እንደ ማክዶናልድ በዝተው ሞልተው ይገኛሉ፡፡ አብዛኞቹ ደግሞ ኢትዮጵያውያን ባልሆኑ ሰዎች የተጻፉ ናቸው፡፡ ሌላው ቢቀር ኤንሪኮ ቼሩሊ የደብረ ሊባኖስ አበ ምኔቶች ታሪክ(Gli Abbati di Dabra Libanos, 1945)፣ ኮንቲ ሮሲኒ ከሐተታ ጋር ያሳተመውን ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት፣በዋልድባ ቅጅ (Il Gadla Takla Haimanot secondo la redazione Waldebbana, 1896)፣ የዊልያም በጅን የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ሕይወትና ተአምር (The Life and Miracles of Takla Haymanot, 1906)፡፡ ከኢትዮጵያውያን ጸሐፍትም ውስጥ የታደሰ ታምራትንChurch and State in Ethiopia, ማንበብ በተገባው ነበር፡፡

Monday 7 October 2013

ቀጣዩ የኢሕአዴግ ዒላማ ማኅበረ ቅዱሳን ይኾን?

FACT Weekily Magazine cover story


(ፋክት መጽሔት፤ ቅጽ 2 ቁጥር 14 መስከረም ፳፻፮ ዓ.ም.

ተመስገን ደሳለኝ

የኢሕአዴግ ታጋዮች የመንግሥት ‹‹ጠንካራ ይዞታ›› የሚባሉ ከተሞችን ሳይቀር መቆጣጠር ችለዋል፤ ወደ አዲስ አበባም የሚያደርጉት ግሥጋሴም ፕሬዝዳንት መንግሥቱ ኃይለ ማርያምን ሳይቀር ዕንቅልፍ ነስቷል፡፡ በአንዳች ተኣምር ግሥጋሴውን መግታት ካልቻሉ በጥቂት ወራት ውስጥ ሁሉም ነገር ታሪክ እንደሚኾን በማወቃቸው መላ በማፈላለጉ ላይ ተጠምደዋል፡፡ በዚህን ጊዜ ነበር(የሐሳቡ አመንጪ ተለይቶ ባይታወቅም)፣ ‹‹ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች አጭር ሥልጠና ሰጥቶ ከሀገሪቱ ሠራዊት ጎን ማሰለፍና የ‹ወንበዴውን ጦር› መድረሻ ማሳጣት›› የሚለው ሐሳብ እንደ መፍትሔ የተወሰደው፡፡

እናም መንግሥቱ ራሳቸው ተማሪዎቹን በዩኒቨርስቲ አዳራሽ ሰብስበው እንዲህ ሲሉ አፋጠጧቸው፡- ‹‹እነርሱ (ኢሕአዴግና ሻዕቢያን ማለታቸው ነው) ለእኵይ ዓላማቸው ከእረኛ እስከ ምሁር ሲያሰልፉ እናንተ ምንድን ነው የምትሠሩት? በሰላማዊ ሰልፍና በስብሰባ ብቻ መቃወም ወይስ ወንበዴዎቹ እንዳደረጉት ከአብዮታዊ ሠራዊታችነ ጎን ቆማችኹ የአገሪቱን ህልውና ታስከብራላችኹ?››

ይህን ጊዜም አስቀድሞ በተሰጣቸው መመሪያ ከተማሪው ጋራ ተመሳስለው በአዳራሹ የተገኙት የደኅንነት ሠራተኞችና የኢሠፓ ካድሬዎች ‹‹ዘምተን ከጠላት ጋራ መፋለም እንፈልጋለን›› ብለው በስሜትና በወኔ እየተናገሩ በሠሩት ‹ድራማ› ተማሪው ትምህርት አቋርጦ እንዲዘምት ተወሰነ፤ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲም ተዘጋ፤ ተማሪዎቹም ለወታደራዊ ሥልጠና ደቡብ ኢትዮጵያ ወደሚገኘው የብላቴ አየር ወለድ ማሠልጠኛከተቱ፡፡

ከመላው ዘማቾች [የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ የኾኑ ሠልጣኞች በማሠልጠኛው ባዶ ድንኳን] በየጊዜው እየተሰበሰቡና በመጨረሻም ካምፓቸው አቅራቢያ ወደሚገኘው ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ከመዐቱ ይታደጋቸው ዘንድ ፈጣሪያቸውን በጸሎት መማጠን የሕይወታቸው አካል አደረጉት፤ ከቀናት በኋላም በአንዱ ዕለት አንድም ለመታሰቢያና ለበረከት. ሁለትም ስብስቡ ሳይበተን ወደፊት እንዲቀጥል በሚል ዕሳቤ ‹‹ማኅበረ ሚካኤል›› ብለው የሠየሙትን የጽዋ ማኅበር መሠረቱ፡፡ . . . ይኹንና ከመካከላቸው አንዳቸውም እንኳ በ፲፱፻፸፯ ዓ.ም በፓዌ መተከል ዞን የተደረገውን የመልሶ ማቋቋም ሠፈራ ፕሮግራም እንዲያመቻቹ በዘመቱ ተማሪዎች ከተመሠረተውና ከተለያዩ የጽዋ ማኅበራት ጋራ በመዋሐድ የዛሬውን ‹‹ማኅበረ ቅዱሳን›› እንደሚፈጥሩ መገመት የሚችሉበት የነቢይነት ጸጋ አልነበራቸውም፤ የኾነው ግን እንዲያ ነበር፡፡

Wednesday 2 October 2013

ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የወጡ (ያፈነገጡ) ሰዎች የሚመለሱት እንዴት ነው?

ዲ/ን ያረጋል አበጋዝ
(ከማኅበረ ቅዱሳን ድህረ ገጽ ላይ ሳይቀነስ ሳይጨመር  የተወሰደ)


፩. የቤተ ክርስቲያን ምንነት፣ ዓላማና ተልእኮዎች

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምትባለው በአጭር ቃል የኢየሱስ ክርስቶስ አካል ስትሆን፣ አማንያን ደግሞ የተለያዩ የአካል ክፍሎቿ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ባለቤቷና መሥራቿ እግዚአብሔር ሲሆን ከእግዚአብሔር ጋር መንፈሳዊ ኅብረትና ግንኙነት ያላቸው መንፈሳውያን አንድነት (ጉባኤ) ናት፡፡ አንድ ሰው በሃይማኖትና በምሥጢራት አማካይነት ወደዚህች ጉባኤ ሲገባ የዚህ ጉባኤ (ኅብረት) አካል ሆኖ ይሠራል፡፡ ሐዋርያው “ወደ ልጁ ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ኅብረት የጠራችሁ እግዚአብሔር የታመነ ነው” በማለት ያስረዳው ይህን ነው፡፡ 1 ቆሮ. 1፡9 እንዲሁም “ከእንግዲህ ወዲህ ከቅዱሳን ጋር ባላገሮችና የእግዚአብሔር ቤተ ሰዎች ናችሁ እንጂ እንግዶችና መጻተኞች አይደላችሁም” የሚለው ቃል ይህን የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ እሳቤ ያሳያል። ኤፌ. 2፡19-22 ይህች እግዚአብሔር የመሠረታት ጉባኤ (ማኅበር) ቀዳማዊት ናት፤ “ተዘከር ማኅበረከ ዘአቅደምከ ፈጢረ - አስቀድመህ የፈጠርሃትን ማኅበርህን አስብ” ያለው ለዚህ ነው፡፡ መዝ. 73፡2

የቤተ ክርስቲያን የአንድነቷ መሠረት ሃይማኖት ነው፡፡ ይህ ሃይማኖት ደግሞ ከእግዚአብሔር የተሰጠ አንድና ብቸኛ እውነት ነው፡፡ ሐዋርያው “ብዘገይ ግን፥ በእግዚአብሔር ማደሪያ ቤት እንዴት መኖር እንደሚገባ ታውቅ ዘንድ እጽፍልሃለሁ፤ ቤቱም የእውነት ዓምድና መሠረት፥ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ነው” ያለው ለዚህ ነው፡፡ 1 ጢሞ. 3፡15 ይህ የቤተ ክርስቲያን አምዷ (ምሰሶዋ) የሆነው እውነትና ሃይማኖት ካልተጠበቀ ወይም ችላ ከተባለና እግዚአብሔር ከገለጠው እውነት ጋር እንሸቃቅጠው ከተባለ ቤተ ክርስቲያን ባሕርይዋ ስለማይፈቅድላት እንዲህ ያለ ነገር መቀበል አትችልም፡፡ የቤተ ክርስቲያን መሠረቷ እና ዓምዷእውነት ነውና፡፡