Saturday 22 March 2014

ሰበር ዜና – የማኅበረ ቅዱሳንን አመራርና አባላት በአክራሪነት የሚከስ ዶክመንተሪ ሊዘጋጅ ነው ተባለ

  • ዶክመንተሪው የ2007 ሀገራዊ ምርጫ ቅድመ ዝግጅት አካል እንደኾነ ተጠቁሟል
  • ‹‹ማስረጃ አቅርቡና እንነጋገርበት›› ለሚለው የማኅበሩ ጥያቄ ምላሽ አልተሰጠም

(ፋክት፤ ቅጽ ፪ ቁጥር ፴፰፤ መጋቢት ፳፻፮ ዓ.ም.)



በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሲኖዶሱን ይኹንታ አግኝቶ በመላው አገሪቱ የሚንቀሳቀሰውን የማኅበረ ቅዱሳንን አመራርና አባላት በአክራሪነት የሚከስ ነው የተባለ ዶክመንተሪ ፊልም ለማዘጋጀት መታቀዱ ተጠቆመ፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አንዳንድ ሓላፊዎች አቀብለውታል በተባለ መረጃ እንደሚታገዝና በመንግሥት አካል እንደሚሰናዳ የተገለጸው የዶክመንተሪ ዝግጅቱ በማኅበሩ ኻያ አመራሮች እና አባላት ላይ እንዳነጣጠረ ተገልጧል፡፡