Friday 24 January 2014

ፓትርያርኩ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በሙስና ላይ እንዲዘምቱ አዘዙ

  • በቤተ ክርስቲያናችን ሸፍጥና ጉቦ ተንሰራፍቷል›› /ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ/
  • ሰንበት ት/ቤቶቹ የአማሳኝ አስተዳዳሪዎችን ዶሴ ለፓትርያርኩ ለማቅረብ ተዘጋጅተዋል
(አዲስ አድማስ፤ ቅጽ ፲፫ ቁጥር ፯፻፴፩፤ ቅዳሜ ጥር ፲ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም.)
His Holiness Patriartch Abune Mathias
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ በተንሰራፋውና ለዕድገቷ መሰናክል ኾኖ በተደነቀረው ሙስናና ሸፍጥ ላይ በተጠናከረ ኃይል በመዝመት የተጀመረውን የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ከዳር እንዲያደርሱ አዘዙ፡፡

ፓትርያርኩ: የቤተ ክርስቲያኒቷ የመዋቅር ለውጥ ሕግ ረቂቅ ‹‹የእኔ ጩኸት ነው›› አሉ

ለአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ የሚሰማው የካህናቱና ምእመናኑ ጩኸት በርክቷል

(ፋክት መጽሔት፤ ቅጽ ፪ ቁጥር ፳፱ ጥር ፳፻፮ ዓ.ም.)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአስተዳደራዊ መዋቅሯ ትክክለኛውን መሥመር ይዛ ወደ ቀደመ የቅድስናና ንጽሕና ክብሯ እንድትመለስ በአደረጃጀትዋና አሠራሯ ላይ እየተካሔደ የሚገኘው የተቋማዊ ለውጥ ጥናት፣ ‹‹ከጅምሩም የእኔ ጩኸት ነው፤ የእኔ አጀንዳ ነው፤ ዛሬ ከደረሰበትም ወደ ኋላ አይመለስም፤›› ሲሉ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ቃል ገቡ፡፡

ፓትርያርኩ ይህን የተናገሩት፣ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ ጥናት ሳይዘገይ ተግባራዊ እንዲኾን ጥያቄ ያቀረቡ የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎችን፣ የጽ/ቤት ሠራተኞችን፣ ካህናትን፣ መምህራንና ምእመናንን ጥር 2ና 5 ቀን 2006 ዓ.ም. በጽ/ቤታቸውና በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ተቀብለው ባነጋገሩበት ወቅት ነው፡፡