Tuesday 31 December 2013

የአ/አ ሀ/ስብከት የአደረጃጀትና አሠራር ጥናት ካህናቱንና ምእመናኑን እያነጋገረ ነው











ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች እንዲያገልግሉ ብቻ ሳይሆን በትምህርትና በተግባራዊ ልምምድ ለከፍተኛ ክብርና ማዕርግ እንዲበቁም ትሠራለች
ገዳማት እና አድባራት የልማት ፈንድ ያቋቁማሉ
/ምንጭ፡- ኢትዮ – ምኅዳር፤ ቅጽ 02 ቁጥር 51፤ ረቡዕ፣ ታኅሣሥ 23 ቀን 2006 ዓ.ም./

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሰሞኑን ለሀ/ስብከቱ ባለድርሻ አካላት ለውይይት ያቀረበው የአደረጃጀትና አሠራር ጥናት ሰነድ ካህናቱንና ምእመናኑን እያነጋገረ ነው፡፡ የጥናት ሰነዱን እንደማይቀበሉት የሚገልጹ ወገኖች፡- ‹‹ጥናቱ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት ያልተሳተፉበትና በውይይት ያልዳበረ በመኾኑ በገለልተኛና ልምድ ባላቸው ምሁራን ይሰናዳ፤ ከነባሩ ሕገ ቤተ ክርስቲያንና ቃለ ዐዋዲ ጋራ የሚጋጭና የሚጣረስ ነው፤›› ይላሉ፡፡
ጥናቱ ‹‹ነባሩን ሠራተኛ በማፈናቀል በስመ ዲግሪና ዲፕሎማ ዕውቀት የሌለውን በመዋቅሩ ውስጥ በመሰግሰግ ቤተ ክርስቲያኒቱን ለመቆጣጠር ያለመ ነው፤›› የሚሉት እኒሁ ወገኖች፣ ‹‹የአጥኚው አካል ማንነት በግልጽ አይታወቅም፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ የመጨረሻ ሥልጣን ያለውን የፓትርያርኩን ሥልጣን ይጋፋል፤›› የሚሉ ተቃውሞዎችን በመዘርዘር አቤቱታቸውን ለፓትርያርኩና ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት አቅርበዋል፡፡

ብጹዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ቴዎፍሎስ

(አንድ አድርገን ታህሣሥ 21 2006 ዓ.ም)፡- 
ኢትዮጵያ ብዙ መከራዎችን አሳልፋለች ፤ ብዙዎቹ መከራዎች ከውጭ ወራሪዎች ቢደረሱም ከውስጥ ሀይሎችም ከደረሰው ጥቃት ያልተናነሰ መከራ በቤተክርስትያንና በሀገር ላይ ብዙ መከራ ደርሷል ፤ ይህች ቤተክርስቲያን ከዘመነ አክሱም ጀምሮ አሁን እስካለንበት የኢህአዴግ ዘመን ድረስ ብዙ መንግስታትን አሳልፋለች ፤ ፈሪሀ እግዚአብሔር ያላቸው ነገስታት ለቤተክርስትያን እና ለህዝበ ክርስትያን በርካታ መልካም ተግባሮችን አከናውነው ወደማይቀረው አለም አልፈዋል ፤ ስማቸውም በየዘመኑ በመልካም እየተጠራ ትውልድም የሚዘክራቸው እስከ አሁን ድረስ አሉ ፤ ሌሎች ደግሞ የምትጠፋ መስሏቸው ጦር መዘውባታል ፤ በዘመናቸው ቤተክርስትያኒቷን ለማፍረስ ድንጋይ አንስተውባታል ፤ አሳት ለኩሰውባታል ፤ እርሷ ግን የመጣውን መከራ ተቋቁማ እጃቸውን ያነሱባትን ወደ ኋላ ትታ አሁን እኛ ትውልድ ላይ ደርሳለች፡፡